አጠቃላይ ጉባኤ
የማካካሻ በረከቶች
የሚያዝያ 2025 (እ.አ.አ) አጠቃላይ ጉባኤ


11:19

የካሳ በረከቶች

በህይወት ውስጥ ብዙ ሁኔታዎች ከአቅማችን በላይ ሊሆኑ ቢችሉም ማናችንም የጌታ ማለቂያ የሌለው በረከቶች ሳይደርሰን አይቀርም።

በኤጲስ ቆጶስነት አመራር በማገልገልበት ወቅት፣ በዓለም ዙሪያ በተለያዩ ቦታዎች እና ባህሎች የሚገኙ የኋለኛው ቀን ቅዱሳንን የማግኘት እድል አግኝቻለሁ። በእናንተ ዘላቂ እምነት እና ለጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ባላችሁ ታማኝነት ያለማቋረጥ ስነሳሳ ነበር። ሆኖም ብዙዎቻችሁ በሚያጋጥሟችሁ የተለያዩ እና ብዙ ጊዜ አስቸጋሪ ሁኔታዎች—እንደ ህመም፣ የአካል ጉዳተኝነት፣ የአቅም ውስንነት፣ ለትዳር ወይም ለትምህርት ያነሱ እድሎች፣ በሌሎች የሚደርስ ጥቃት እና ሌሎች እክሎች ወይም ገደቦች ያሉ ተግዳሮቶች ተነክቻለሁ። አንዳንድ ጊዜ፣ እነዚህ ፈተናዎች እድገታችሁን የሚገቱ ሊመስሉ እና ወንጌልን በተሟላ ሁኔታ ለመኖር የምታደርጉትን እውነተኛ ጥረት የሚፈታተኑ ሊመስሉ ይችላሉ፣ ይህም ለማገልገል፣ ለማምለክ እና ቅዱስ ሀላፊነቶችን ለመወጣት የበለጠ ከባድ ያደርገዋል።

ውድ ጓደኞቼ፣ በህይወታችሁ በሁኔታዎች የተገደባችሁ ወይም የተጎዳችሁ እንደሆነ ከተሰማችሁ፣ ጌታ በግል እንደሚወዳችሁ እንድታውቁ እፈልጋለሁ። ሁኔታዎቻችሁን ያውቃል እንዲሁም ምንም አይነት ፈተና ቢገጥማችሁ የበረከቱ በር ለእናንተ በሰፊው ክፍት ሆኖ ይቆያል።

ይህን እውነት የተማርኩት ምንም እንኳን ቀላል ቢመስልም በእኔ ላይ ዘላቂ ተጽእኖ ባሳደረው የግል ተሞክሮዬ ነው። በ22 ዓመቴ፣ በፓሪስ የፈረንሳይ አየር ኃይል ውስጥ እያገለገልኩ ሳለ፣ የጌታ ሐዋርያ ሽማግሌ ኒል ኤ. ማክስዌል በቻምፕስ-ኤሊሴስ ኮንፈረንስ ላይ እንደሚናገሩ በማወቄ በጣም ደስ ብሎኝ ነበር። ይሁን እንጂ፣ ዝግጅቱ ከመጀመሩ ጥቂት ቀደም ብሎ ጉባኤው በሚካሄድበት በተመሳሳይ ሰዓት ላይ አንድ ከፍተኛ መኮንን በመኪና ወደ አየር ማረፊያው እንድወስደው ትእዛዝ ደረሰኝ።

በጣም አዘንኩ። ለመገኘት ቆርጬ በመነሳት፣ መኮንኑን አድርሼው ወደ ኮንፈረንሱ በችኮላ ሄድኩ። የመኪና ማቆሚያ ቦታ ካገኘሁ በኋላ፣ ሻምፕስ-ኤሊሴስን በፍጥነት ተጉዤ ወደ መሰብሰቢያው ቦታ ስብሰባው ሊጠናቀቅ አምስት ደቂቃ ሲቀረው እስትንፋስ እያጠረኝ ደረስኩ። ልክ እንደገባሁ፣ ሽማግሌ ማክስዌል፣ “አሁን የሐዋርያዊ በረከትን እሰጣችኋለሁ” ሲሉ ሰማሁ። በዚያ ቅጽበት፣ ቆንጆ፣ የማይረሳ መንፈሳዊ አጋጣሚ ነበረኝ። በመንፈስ ተሞልቼ የበረከቱ ቃላቶች ለእኔ ብቻ የታሰቡ በሚመስል ሁኔታ ወስጤ ሰርገው ገቡ።

የዚያን ቀን ያጋጠመኝ ነገር ትንሽ ነገር ግን ኃያል የሆነ የእግዚአብሄር ለልጆቹ እቅድ አፅናኝ መገለጫ ነበር፦ ከአቅማችን በላይ የሆኑ ሁኔታዎች የልባችንን የጽድቅ ፍላጎቶች እንዳንፈጽም ሲከለክሉን፣ ጌታ የገባውን በረከቶች እንድንቀበል በሚያስችሉን መንገዶች ይካስናል።

ይህ የሚያረጋጋ እውነት ዳግም በተመለሰው የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል ውስጥ በሚገኙ ሦስት ቁልፍ መርሆች ላይ የተመሰረተ ነው።

  1. እግዚአብሔር እያንዳንዳችንን በፍጹምነት ይወደናል። “ሁላችንም ወደ እርሱ እንድንመጣ እና ከቸርነቱ እንድንካፈል ይጋብዛል።” የእርሱ የቤዛነት እቅድ ሁሉም ሰው፣ ያለ ምንም ልዩነት፣ አንድ ቀን የመዳን እና ከፍ ከፍ የመደረግ በረከቶችን ለመቀበል ፍትሃዊ እድል እንደሚሰጠው ያረጋግጣል።

  2. እግዚአብሔር ፍትሃዊ እና መሐሪ ስለሆነ እና እቅዱ ፍጹም ስለሆነ፣ ከቁጥጥራችሁ በላይ በሆኑ ነገሮች ተጠያቂ አያደርገንም። ሽማግሌ ኒል ኤ. ማክስዌል እንዳብራሩት “እግዚአብሔር… ፍላጎታችንን እና አድራጎታችንን ብቻ ሳይሆን የተለያዩ ሁኔታዎች በኛ ላይ የሚጭኑብንን ችግሮችንም ግምት ውስጥ ያስገባል።”

  3. በኢየሱስ ክርስቶስ እና በኃጢያት ክፍያው አማካኝነት ሁሉንም የህይወት ፈተናዎች ለመፅናት እና ለማሸነፍ ጥንካሬን ማግኘት እንችላለን። አልማ እንዳስተማረው፣ አዳኙ ንስሃ የገቡትን ኃጢአቶች ብቻ ሳይሆን “የህዝቡን ስቃይ እና ህመም” እንዲሁም “ድካማቸውን” ወስዷል። ስለዚህ፣ ከስህተታችን ከመቤዠታችን ባሻገር፣ የጌታ ምህረት እና ፀጋ በምድራዊ ልምምዳችን በተጫኑ ኢፍትሃዊነት፣ ጉድለቶች እና ገደቦች ይደግፈናል።

እነዚህን የካሳ በረከቶችን መቀበል በተወሰኑ ሁኔታዎች ላይ ይወሰናል። ጌታ “የምንችለውን ሁሉ እንድናደርግ” እና “ሙሉ ነፍሳችንን ለእርሱ እንደ መስዋዕት እንድናቀርብ ይጠይቀናል።” ይህ ጥልቅ ፍላጎትን፣ ቅን እና ታማኝ ልብን እና ትእዛዛቱን ለመጠበቅ እና ፈቃዳችንን ከእሱ ጋር ለማስማማት ያለንን ከፍተኛ ትጋት ይጠይቃል።

ከአቅማችን በላይ በሆኑ ሁኔታዎች ምክንያት ከልብ የሆነው ጥረታችን እንዲሆን ለምንፈልገው በቂ ሳይሆን ሲቀር ጌታ አሁንም የልባችንን ፍላጎት እንደ ብቁ መስዋዕት አድርጎ ሊቀበል ይችላል። ፕሬዚዳንት ዳለን ኤች. ኦክስ እንዳስተማሩ፣ “አንዳንድ የውጭ ሁኔታዎች ምኞቶቻችንን ወደ ተግባር ማዋል እንዳንችል ቢያደርጉንም ለልባችን የጽድቅ ፍላጎቶች እንባረካለን”።

ነቢዩ ጆሴፍ ስሚዝ አስፈላጊ የወንጌል ስርዓቶችን ሳይቀበል ስለሞተው ወንድሙ አልቪን እየተጨነቀ ሳለ፣ ይህንን የሚያጽናና ራዕይ ተቀበለ፡- “በሙሉ ልባቸው [ወንጌሉን] ይቀበሉ የነበሩ፣ ካለዚህ እውቀት ከዚህ በኋላ የሞቱት ሁሉ [የእግዚአብሔር የሰለስቲያል መንግስት] ወራሾች ይሆናሉ።” ጌታም “እኔ ጌታ ሁሉንም ሰዎች በስራዎቻቸው መሰረት፣ እንደልባቸውም ምኞት እፈርድባቸዋለሁና።”በማለት አክሏል።

ለጌታ አስፈላጊ የሆነው መቻላችን ብቻ ሳይሆን እርሱን እንደ አዳኛችን ለመከተል የምንችለውን ሁሉ ለማድረግ ፈቃደኛ መሆናችንም ጭምር ነው።

በአንድ ወቅት አንድ ወዳጅ ከልብ የመነጨ ጸሎት ቢያደርግም እና ከልብ የማገልገል ፍላጎት ቢኖረውም በጤና ምክንያት ቀደም ብሎ ወደቤቱ እንዲመለስ በመደረጉ ያዘነን ወጣት ሚስዮናዊ አጽናንቶታል። ጌታ “የሰዎች ልጆች ሁሉ በሙሉ ሀይላቸውና ባላቸው ሁሉ ያንን ስራ ቢፈጽሙ፣ እና ቅንነታቸውን ባያጎድሉ፣ እና ጠላቶቻቸው [በህይወታችን ውስጥ ያሉ መጥፎ ሁኔታዎችን ጨምሮ]… ቢመጡባቸው እና ያንንም ስራ እንዳያከናውኑ እንቅፋት ቢሆኑባቸው፣ እነሆ፣ ከእነዚያ የሰዎች ልጆች እጆች ላይ ያንንም ስራ በተጨማሪም ላለመጠየቅ፣ ነገር ግን መስዋዕታቸውን እቀበል ዘንድ ፍቃዴ ነው” በማለት የተናገረውን ጥቅስ አካፈለ።

ጓደኛዬ የማገልገል ጥሪውን ተቀብሎ የተቻለውን ሁሉ እንዳደረገ እግዚአብሔር እንደሚያውቅ ለወጣቱ መሰከረለት። ጌታ መባውን እንደተቀበለ እና ለሁሉም ታማኝ ሚስዮናውያን ቃል የተገባላቸው በረከቶች እንደማይከለከሉ አረጋገጠለት።

የጌታ የካሳ በረከቶች ብዙ ጊዜ የሚመጡት በራሳችን ልናደርገው የማንችለውን እንድንፈፅም በሚረዱን በሌሎች ደግነት እና አገልግሎት አማካኝነት ነው። በፈረንሳይ ከምትገኝ ሴት ልጃችን ርቀን እንኖር በነበርንበት ወቅት ከከባድ ወሊድ በኋላ እርሷን ለመርዳት አቅም አጥተን የነበርንበትን ጊዜ አስታውሳለሁ። በዚያው ሳምንት፣ በዩታ የሚገኘው አጥቢያችን መንታ ልጆችን ለወለደች እናት እርዳታ ጠየቀ። ባለቤቴ ቫሌሪ ለአዲስ እናት እና ለተቸገረችው ልጃችን በልቧ ጸሎት በመጸለይ ለእርሷ ምግብ ለማቅረብ ፈቃደኛ ሆነች። ብዙም ሳይቆይ፣ በፈረንሳይ በልጃችን አጥቢያ ውስጥ ያሉ እህቶች ለቤተሰቧ ምግብ ለማቅረብ መደራጀታቸውን አወቅን። እኛ ባልቻልንበት ጊዜ መጽናናትን እንዲያመጡ እግዚአብሔር መላእክቱን በመላክ ጸሎታችንን መለሰልን።

ውስንነቶች እና ተግዳሮቶች ሲያጋጥሙን የራሳችንን በረከቶች—ስጦታዎቻችንን፣ ሀብታችንን እና ጊዜያችንን—በማወቅ የተቸገሩትን ለማገልገል እንጠቀም። ይህን ስናደርግ ሌሎችን መባረክ ብቻ ሳይሆን ፈውስ እና ካሳ ወደ ህይወታችን እንጋብዛለን።

ለእግዚአብሔር የካሳ በረከቶች ማበርከት ከምንችልባቸው በጣም ሀይለኛ መንገዶች መካከል አንዱ ለቅድመ አያቶቻችን በጌታ ቤት በምንሰራው የውክልና በጎ ተግባር ነው። በምድራዊ ህይወታቸው እነርሱን ለመቀበል እድል ላላገኙ በረከቶችን ለመስጠት ስጦታዎቻችንን እና ችሎታዎቻችንን በመጠቀም በእነርሱ ምትክ ስርዓቶችን በምንፈጽምበት ጊዜ፣ በጌታ ታላቅ የማዳን ስራ ውስጥ በንቃት እንሳተፋለን።

በቅዱስ ቤተመቅደሶች ውስጥ የምናደገው የፍቅር አገልግሎት የአዳኙ ጸጋ ከዚህ ህይወት በላይ እንደሚዘልቅ ያስታውሰናል። በሚመጣው ህይወት በምድራዊ ህይወት ማድረግ ያልቻልነውን ለመፈጸም አዲስ እድሎችን ሊሰጡን ይችላሉ። ፕሬዚዳንት ሎሬንዞ ስኖው ዘላለማዊ አጋርን ገና ላላገኙ እህቶች ሲናገሩ በፍቅር እንዲህ አሉ፡- “ታማኝ ህይወት ከኖረ በኋላ የሚሞት የኋለኛው ቀን ቅዱሳን እርሱ ወይም እርሷ እድሎች ባልተሟሉበት ጊዜ አንዳንድ ነገሮችን ማድረግ ባለመቻላቸው ምክንያት ምንም ነገር አያጣጡም። … ይህንን እድል ያገኙ ወንድ ወይም ሴት የሚያገኘውን ሁሉንም በረከቶች፣ ከፍ ከፍ መደረግ እና ክብር ያገኛሉ።”

ይህ የተስፋና የመጽናናት መልእክት ለሁላችንም የእግዚአብሔር ልጆች ነው። ማናችንም ብንሆን ከምድራዊ ህይወት ፈተናዎች እና ጉድለቶች ማምለጥ አንችልም። ሁላችንም የተወለድነው እራሳችንን ለማዳን በማንችልበት ተፈጥሯዊ ጉድለት ነው። ሆኖም፣ አፍቃሪ አዳኝ አለን እንዲሁም “በጸጋ[ው] የምንድነው የምንችለውን ካደረግን በኋላ እንደሆነ እናውቃለን።”

በህይወት ውስጥ ብዙ ሁኔታዎች ከአቅማችን በላይ ሊሆኑ ቢችሉም ማናችንም የጌታ ማለቂያ የሌለው በረከቶች ሳይደርሰን እንደማይቀር እመሰክራለሁ። በእርሱ የኃጢያት ክፍያ መስዋዕትነት፣ ነፍሳችንን በሙሉ ለእርሱ ከሰጠን አዳኙ ለእያንዳንዱ ጉድለት እና ኢፍትሃዊነት ይክሰናል። በኢየሱስ ክርስቶስ ስም፣ አሜን።