እምነት፦ የመተማመን እና ታማኝ የመሆን ትስስር
በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ስንታመን እምነት እንደሚበቅል እና ለእርሱ ታማኞች ስንሆን ደግሞ እምነት እንደሚያብብ አስተውሉ።
አስራሰባት አመቴ ሳለ፣ ለጓደኛዬ ጆሲ ሊዊዝ እንዴት መዋኘት እንደሚቻል ላስተምረው ቃል ገባሁለት። ስለዚህ አንድ ረፋድ ጠዋት ላይ የምንለማመድበትን ጊዜ ወሰንን። ትምህርታችን አብቅቶ የመዋኛ ገንዳውን ትቼ ስወጣ፣ ጓደኛዬ እርዳታ ለማግኘት ሲጣራ ሰማሁት። በመዋኛ ገንዳው ወደ ጥልቁ ውስጥ እየሰመጠ ነበር።
እርዳታን ለማጝኘት እየፀለይኩኝ ወደውሃው ተወርውሬ ወደ እርሱ ዋኘሁኝ። ወደዳርቻ ጎትቼ ላወጣው እጁን ስይዘው፣ በጣም የተደናገጠው ጓደኛዬ ጀርባዪ ላይ ወጣና መተንፈስ ወደማልችልበት አደገኛ ሁኔታ ላይ ከተተኝ። አሁን ሁለታችንም እየሰመጥን ነበር። ወለሉ ላይ ለመውጣት የቻልኩትን ያህል እየጣርኩኝ፣ ተአምር ከአምላክ እንዲመጣ በሙሉ ሃይሌ ጸለይኩኝ። ከዚያም በኋላ፣ ፣ አንድ እጅ ወደ መዋኛ ገንዳው ጫፍ ይዞኝ፣ ደህንነት ወዳለበት ቦታ ሲወስደን በቀስታ ነገር ግን ያለማቋረጥ የእግዜአብሔር ሃይል ተገለጠ።
ይህ ተሞክሮ ፕሬዚዳንት ራስል ኤም. ኔልሰን በአንድ ወቅት እንዲ ሲሉ ያስተማሩትን ጥልቅ ትምህርት ያረጋግጣል- “የእግዚአብሔርን ሃይል በህይወታችሁ ለመጠቀም ስትጥሩ ልክ በዉሃ ውስጥ ሊሰጥም ያለ ሰው አየር ለማግኘት እንደሚታገለው እና አየርም ሲያገኝ ሃይል እንደሚኖረው ሁሉ የክርስቶስም ሃይል የእናንተ ይሆናል።
ውድ ልጆች እና ወጣቶች፣ ዛሬ በክርስቶስ ላይ ስላለ እምነት አስፈላጊ መርህ ላነጋግራችሁ እወዳለሁ።
በክርስቶስ ላይ እምነት መኖር ማለት በእርሱ መተማመን ማለት ነው።
በኢየሱስ ክርስቶስ ማመን ምን ማለት ነው? በእርሱ እናምናለን ወይም እርሱ እውን እንደሆነ ምስክርነት አለን ማለት ነው? ይህ ጅማሬ ሊሆን ይችላል፣ ነገር ግን ከዚያም በላይ ነው። እምነትን እንደ መተማመን አድርጋችሁ አስባችሁ ታውቃላችሁ? በጣም ስለምታምኑት ሰው አስቡ—ምን አልባትም የቤተሰብ አባል ወይም ጓደኛ። የምታምኗቸው ለምንድንነው? ይህ ሊሆን የቻለው፣ ተከታታይነት ያለውን የእነርሱን ፍቅር እና እርዳታስላያችሁ ነው።
በክርስቶስ ላይ እምነት ሲኖረን፣ የእርሱን በረከቶች እናስተውላለን እንዲሁም የመተማመን ግንኙነትን ከእርሱ ጋር እንመሰርታለን።
በክርስቶስ ላይ ያላችሁን እምነት ማሳደግ የምትችሉት እንዴት ነው?
በቅርብ በተደረገው የወጣቶች የሃይማኖት ትምህርት ላይ፣ በሕይወታችሁ ውስጥ የሰማያዊ ብርሃን ጨረር ስለተቀበላችሁበት ጊዜ እንድታሰላስሉ ተጋብዛችሁ ነበር።” ይህንን ልምምድ ሞክሩ!
ስለክርስቶስ እንዲሁም የእርሱ ወንጌል እና የሐጢያት ክፍያው ወደህይወታችሁ ስለሚያመጣው ደስታ በማሰላሰል ጀምሩ። በተጨማሪም፣ እግዚአብሔር ለእናንተ፣ ለምትወዷቸው እና በቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ለተጠቀሱት ሰዎች በመከራ ጊዜ የደረሰበትን ጊዜ የሚዘግብ ትርጉም የሚሰጡ “የመንፈሳዊ ነገሮች ማስታወሻ” ያዙ። አሁን፣ መንፈስ ቅዱስ በልባችሁ “ጽላት” ላይ እነዚህን እስክትቀርጹ ድረስ እነዚህ ምስክርነቶች ወደህይወታችሁ ሃይልን ሊያመጡ አይችሉም። ስለዚህ እነዚህ ተአምራት በትክክለኛው ጊዜ እንዲመጡ እግዚአብሔር ያስቀመጣቸውን ነገሮች ሁሉ አስቡ እና መዝግቡ።
ይህንን ልምምድ ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብ የሚሆን አጋጣሚ አድርጋችሁ ውሰዱት። ልክ የመጀመሪያ ጊዚያችሁ የሆነ ይመስል ወደ የሰማይ አባታችሁ ጸልዩ። ስለበረከቶቹ ያላችሁን ምስጋና እና ፍቅር ግለጹ። እርሱ ስለእናንተ ምን እንደሚሰማው እና ሕይወታችሁ እያመራው ስላለበት አቅጣጫ ምን እንደሚሰማው እንኳን ሳይቀር ጠይቁት።
ቅን እና ትሁት ከሆናችሁ፣ የእርሱን መልስ ትሰማላችሁ ከዚያም ከሰማይ አባት እና ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ግላዊ እና ዘላቂ የሆነ ግንኙነት ትጀምራላችሁ። ይህ ብቻ ሳይሆን፣ ሃይማኖታዊ የሆኑ የዘውትር ተግባራችሁ ሳይቀሩ ትርጉም ያላቸው ይሆናሉ!! ለምሳሌ፣ መጸለይ፣ የግል ጥናታችሁን ማድረግ እና የቤተመቅደስ አምልኮዎችን ማከናወን፣ እነርሱን ለማወቅ እና ከእነርሱ ጋር ለመሆን እድል እንደሆነ ቆጥራችሁ፣ እነዚን ነገሮች ለመተግበር ትጓጓላችሁ።
እምነት ታማኝ በመሆን ያብባል
በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ስንታመን እምነት እንደሚበቅል እና ለእርሱ ታማኞች ስንሆን እንደሚያብብ አስተውሉ። ከክርስቶስ ጋር እውነተኛ ጓደኝነት የምትፈልጉ ከሆነ፣ ቃልኪዳኖችን በመግባት፣ በታማኝነት እና በክብር በመጠበቅ አሳዩት። ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ቃልኪዳን መግባት ተስፋን ይገነባል። እነሱን ማክበር እምነትን ይገነባል።
የግል ምሳሌን ልጠቀም፦ ልጅ ሳለሁኝ፣ አንድ ቀን እናቴ ብቻዋን ስታለቅስ አገኘሃት። እያለቀሰች የነበረችው ለምን እንደሆነ ስጠይቃት፣ በእርጋታ እንዲህ አለችኝ፣ “ጥሩ ልጅ እንድትሆን እፈልጋለሁ።” የጭንቀቷ ምክንያት እኔ እንዳልሆንኩ ባውቅም እንኳን፣ እናቴን ከማንም በላይ እወድና አምን ነበር እንዲሁም የሕይወቷን ተግዳሮቶች ለመቀነስ እፈልግ ነበር። ስለዚህ፣ አይኖቼ እምባ ቋጥረው እንዲሁም የዘጠኝ አመት ልጅ ሊኖረው በሚችለው አክብሮት፣ በዛን ቀን ሁልጊዜ የተሻልኩኝ ልጅ ለመሆን እና እርሷን ለማኩራት እንደምጥር ቃል ገባሁላት።
ያ ቃል ኪዳን በእኔ ላይ የነበረውን ሃይል—እንዲሁም አሁንም ድረስ በእኔ ላይ ያለውን ሃይል ልታስቡ ትችላላቹሁ?
ከእርሷ ጋር ያደረኩት ያ ቃል ኪዳን ሕይወቴን የሚመራ ነበር። ውሳኔዎችን ከመወሰኔ በፊት፣ ተግባሬ እሷን ያስደስታል አያስደስትም የሚለውን ግምት ውስጥ አስገባለሁ። የዚህ ቃልኪዳን ትስስስር እና ከእናቴ ጋር ያለኝ ግንኙነት ሕይወቴን በሙሉ ላደርኳቸው ተግባራቶች መልሕቅ ነበሩ።
ከአመታት በኋላ፣ ኢየሱስ ክርስቶስን ይበልጥ እያወኩት ስመጣ፣ እምነቴን በእርሱ ላይ የተመሰረተ ማድረግን አውቄ ነበር። ከጌታ ጋር ቃል ኪዳን ገባሁ፣ እነርሱን ለመጠበቅ ስጥርም፣ እስከ ጥግ ድረስ ሐጢያቶቼን ሙሉ ለሙሉ ይቅር ብሏል፣ ሕይወቴን መርቷል፣ እንዲሁም “በፍቅሩ ሞልቶኛል”። ክርስቶስ ለእርሱ ጥልቅ የሆነ ፍቅር፣ ክብር እና ታማኝነትን በውስጤ አስርጿል።
“እምነት የተግባር መርህ” የሆነበትን፣ እና “ያለእምነት [አምላክን] ማስደሰት የማይቻልበትን” ምክንያት ትረዳላችሁ?
እርሱን ደስ የሚያሰኙትን ነገሮች ለማድረግ ስትሞክሩ፣ ዮሴፍ በግብፅ ሣለ በጶጢፋር ሚስት በተፈተነ ጊዜ፣ “እንዴት ይህን ትልቅ ክፉ ነገር አደርጋለሁ? በእግዚአብሔር ፊት እንዴት ኃጢአትን እሠራለሁ?” እንዳለው እናንተም እንደዚያ ትላላችሁ። ወጣቱ ነቢይ ጆሴፍ ስሚዝ ተቃርኖ ባጋጠመው ጊዜ፣ በድፍረት፦ “እኔ አውቄዋለሁ፣ እናም እግዚአብሔር እንዳወቀው አውቄዋለሁ፣ እናም ልክደው አልችልም፤ … ይህንን ባደርግ እግዚአብሔርን እንደማሳዝን አውቃለሁኝ” ብሎ እንዳለው እናንተም እንደዚያ ትላላችሁ።
ስለዚህ በኢየሱስ ክርስቶስ ማመን በመታመን ትስስር ውስጥ በታማኝነት እና በፍቅር የተመሰረተ ነው። በሌላ አባባል፣ እግዜአብሔርን ስለመሃሪ ፍቅሩ (hesed[ሄሴድ]) በማመስገን፣ ትዛዛቱን በመጠበቅ ታማኝ የሆነውን ፍቅራችንን (emunah[ኢሙና]) እናሳያለን።
ጌታ ይህንን ቃል ገብቷል፦ “ትዕዛዜ በእርሱ ዘንድ ያለችው የሚጠብቃትም የሚወደኝ እርሱ ነው፤ የሚወደኝንም አባቴ ይወደዋል እኔም እወደዋለሁ ራሴንም እገልጥለታለሁ።” ለእርሱ ታማኝ ለመሆን ቆራጥ ከሆናችሁ እርሱ ለእናንተ ያለውን ፍቅር ያሳያል።
በመከራ ፊት እምነት
ነገር ግን የግድ የእርሱን ተአምራት ለሚፈልጉ ለእንደዚህ አይነት ፈታኝ ሁኔታዎች ምላሽ መስጠት ያለባችሁ እንዴት ነው? መከራዎች የማይቀየሩ እና አንዳንዴም አስፈሪ ሆነው ሳለ፣ የ2025 (እ.አ.አ) የወጣቶች ጥንካሬ ጭብጥ መፈክር እንደሚጋብዘው፣ ሳትፈሩ ወደእርሱ በቀላሉ ተራመዱ፣ ”ባሰባችሁበት ነገር ሁሉ [ወደእርሱ] ተመልከቱ፣ አትጠራጠሩ፣ አትፍሩ።”
ሳትፈሩ ወደእርሱ መራመድ የምትችሉት እንዴት ነው?
እራሳችሁን በማይታወቅ ቦታ ነገሮችን የሚቃኝ እንግዳ አድርጋችሁ አስቡ። ፊት ለፊታችሁ ያለውን መሰናክል ለማለፍ የብርሃን ምንጭ ያስፈልጋችኋል። ለእግዚአብሔር ያላችሁ ታማኝነት እና ከእርሱ ጋር ያላችሁ የማያቋርጡ ግንኙነቶች ለፋኖሣችሁ ዘይት ነው። ስለዚህ ጨለማ እና አደገኛ ሁኔታዎች ሲያጋጥሟችሁ፣ በጭፍን ወደ እነርሱ ከመራመድ ይልቅ፣ እርግጠኛ ባልሆነው መንገድ ላይ የተስፋ ጭላንጭሎችን ለማፍሰስ በክርስቶስ ላይ ባለው የእምነት ዘይት የተሞላውን ፋኖሳችሁን ታበራላችሁ። ያለፈው ልምዳችሁ፣ ጌታ በጉዞዎቻችሁ እንደሚደግፋችሁ ያላችሁን ተስፋ ይጨምራል።
በክርስቶስ ላይ ባላችሁ ተስፋ እና እምነት ምን ያህል ትጓዛላችሁ?
በመዋኛው ገንዳ ላይ የነበረኝን ታሪክ አስታወሳችሁ? በዚያ ተስፋ አስቆራጭ ወቅት፣ ተአምሩ የመጣው እኔ በጠበኩት መንገድ ነበር፣ ነገር ግን እግዚአብሔር ሁልጊዜ ነገሮች እንደፈቃዳችን እንደሚሆኑ ዋስትና አይሰጥም። እምነታችን ክርስቶስን ማእከል ያደረገ መሆን ሳለበት፣ ተስፋችን ደግሞ እርሱ ሊልካቸው ፈቃደኛ በሆነ ጊዜ በበረከቶቹ ላይ መሆን አለባቸው። “ተአምራትን ጠብቁ፣” ነገር ግን “እግዚአብሔር በሕይወታችን እንዲያሸንፍ እንፍቀድ።”
እግዚአብሔር ለታማኝ ህዝቡ የገባቸው ቃል ኪዳኖች
የእኔ ታናናሽ ወጣት ጓደኞች፣ ምን ያህል እንደምናምናችሁ እና እንደምንወዳችሁ! እናንተ እውነተኛ ስፍራቹ በእግዚአብሔር ቤተሰብ መሃከል ነው እናም ደግሞ የቃል ኪዳኑ ልጆች ናችሁ። በኢየሱስ ክርስቶስ እመኑ እና ታስፋችሁን በእርሱ ላይ አድርጉ። በእውነትም የእርሱ ደቀመዛሙርት እንድትሆኑ ያስችላችኋል።
ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ያላችሁን ግንኙነት ማሳደጋችሁን ዛሬ እንድትጀምሩ እጋብዛችኋለሁ። እርሱን መቼም ላለመተው ቃል ግቡ።
በክርስቶስ ላይ ያላችሁ ታማኝነት፣ ፍቅር እና እምነት ባህሪያችሁን እና ማንነታችሁን ልክ እንደ እርሱ እንዲሆን አድርጎ ይቀርፃል። ። የሰይጣንን ጥቃቶች ማሸነፍ እንድትችሉ በራስ መተማመን እና ጥንካሬን ታገኛላችሁ። እንዲሁም፣ ስትሳሳቱ የእርሱን ምህረት ትመኛላችሁ። በስተመጨረሻም፣ የወደፊት ተስፋችሁ ብሩህ ይሆናል። በእርሱ ፊት ተመልሶ ለመቆም በሚያስችል ሀይል እንኳን ሳይቀር፣ ከእናንተ የሚጠብቀውን ማንኛውንም ነገሮች ሃይሉን ተጠቅማችሁ መፈጸም እንደምትችሉ ይተማመንባችሃል።
“የቤዛነት ፍቅር መዝሙርን” በመዘመር እና “በእርሱ በዘለዓለማዊው ፍቅር ክንዶች [በመከበብ]” ስለሚያገኘው ደስታ እመሰክርላችኋለሁ። ቅዱስ በሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ ስም፣ አሜን።