አዳኙን ለመገናኘት ግላዊ ዝግጅት
የአዳኙን አስተምህሮቶች ተከተሉ። የእርሱ መመሪያዎች ሚስጥራዊ ወይም ውስብስብ አይደሉም። እነሱን ስንከተላቸው መፍራት ወይም መጨነቅ አይገባንም።
ባለፈው ጥቅምት ፕሬዚዳንት ኔልሰን “አሁን እኔ እና እናንተ ለጌታችንና ለአዳኛችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም ምፅዓት የምንዘጋጅበት ጊዜ ነው” በማለት አስተምረው ነበር። ፕሬዚዳንት ኔልሰን ስለ ዳግም ምፅዓት ሲናገሩ ሁል ጊዜም ደስታ በተሞላበት ተስፋ ነው። ሆኖም፣ በመጀመሪያ ክፍል የምትገኝ አንዲት ልጅ ስለ አዳኙ ዳግም ምፅዓት በተነሳ ቁጥር እንደምትጨነቅ ነገረችኝ። “የምፈራበት ምክንያት ኢየሱስ ዳግም ከመምጣቱ በፊት መጥፎ ነገሮች ስለሚከሰቱ ነው” ብላለች።
እንዲህ ሊሰማቸው የሚችለው ልጆች ብቻ አይደሉም። ለእሷ፣ ለእናንተ እና ለእኔ በጣም ጥሩው ምክር የአዳኙን ትምህርቶች መከተል ነው። የእርሱ መመሪያዎች ሚስጥራዊም ውስብስብም አይደሉም። እነሱን ስንከተላቸው መፍራት ወይም መጨነቅ አይገባንም።
በምድራዊ አገልግሎቱ መጨረሻ ላይ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ መቼ ዳግም እንደሚመጣ ተጠይቆ ነበር። በዳግም ምጽአቱ ወይም ከዚህ ዓለም በምንለይበት ጊዜ እርሱን ለመገናኘት እንዴት መዘጋጀት እንዳለብን መልስ ሲሰጥ፣ በማቴዎስ 25 ላይ ተመዝግበው የሚገኙትን ሦስት ምሳሌዎች አስተምሯል። ከእርሱ ጋር ለመገናኘት የሚደረግ የግል ዝግጅት የህይወት አላማ ማዕከል ስለሆነ እነዚህ ትምህርቶች ወሣኝ ናቸው።
በመጀመሪያ አዳኙ የአሥሩን ደናግላን ምሳሌ ተናገረ። በዚህ ምሳሌ አሥር ደናግላን ወደ ሰርግ ግብዣ ይሄዳሉ። አምስቱ በልባምነት ለመብራታቸው የሚሆን ዘይት ገዝተው የነበረ ሲሆን አምስቱ በስንፍና ሳይገዙ ቀሩ። ሙሽራው እንደሚመጣ በተነገረ ጊዜ ሰነፎቹ ደናግላን ዘይት ለመግዛት ሄዱ። ሲመለሱ በጣም ዘግይተው ስለነበር የግብዣው ቤት በር ተዘግቶ ነበር።
ኢየሱስ እኛን ለመርዳት የምሳሌውን ሦስት ገጽታዎች ገልጿል። እንዲህም ሲል አብራርቷል፦
“እናም በክብሬ በምመጣበት በዚያም ቀንም፣ ስለ አሥሮቹ ደናግል የተናገርኩት ምሳሌም ይፈጸማል።
“እነርሱ ጥበበኛ ናቸው እናም እውነትን ተቀብለዋልና፣ እና እንደ መሪያቸውም መንፈስ ቅዱስን ተቀብለዋል፣ እና አልተታለሉም—በእውነት እንዲህ እላችኋላሁ፣ ቀኑን ይዋጃሉ እንጂ ተቆርጠው ወደ እሳቱ አይጣሉም።”
በሌላ አነጋገር፣ እነርሱ አይፈሩም ወይም አይጨነቁም ምክንያቱም ይድናሉ እንዲሁም ይበለፅጋሉ። ያሸንፋሉም።
ልባሞች ከሆንን በክህነት ሥርዓቶች እና በቃል ኪዳኖች አማካኝነት የኢየሱስ ክርስቶስን ወንጌል በመቀበል እውነትን እናገኛለን። በመቀጠልም፣ መንፈስ ቅዱስ ሁልጊዜ ከእኛ ጋር ይሆን ዘንድ ብቁ በመሆን ለመቀጠል እንጥራለን። ይህን አቅም እያንዳንዳችን በግል ቀስ በቀስ ማግኘት ይኖርብናል። ቋሚ፣ ግላዊ የአምልኮ ተግባራት መንፈስ ቅዱስ እንዲመራን ይጋብዛሉ።
ኢየሱስ ጎላ አድርጎ የገለጸው ሦስተኛው ነገር መሳትን ማስወገድ ነው። አዳኙ፦
“ማንም እንዳያስታችሁ ተጠንቀቁ፤
“ብዙዎች በስሜ—እኔ ክርስቶስ ነኝ—በማለት ይመጣሉና፣ እና ብዙዎችንም ያስታሉ።” በማለት አስጠንቅቋል።
አዳኙ፣ አስመሳዮች የተመረጡትን ለማታለል እንደሚሞክሩ እና ብዙ ደቀመዛሙርት እንደሚያስቱ ያውቃል። በሐሰት መለኮታዊ ሃይል እንደተቀበሉ የሚናገሩትን ወይም ጥበብን ወይም ምሪትን አስተማማኝ ካልሆነ ቦታ ወይም ከሚያስቱ ምንጮች የሚቀበሉትን ማመን የለብንም።
መፅሐፈ ሞርሞን አታላዮችን ከደቀመዛሙርት እንዴት መለየት እንደምንችል ያስተምረናል። ደቀ መዛሙርት ሁል ጊዜ በእግዚአብሔር ማመንን፣ እርሱን ማገልገልን እና መልካም ማድረግን ያበረታታሉ። ከሚታመኑ የአዳኙ ደቀመዛሙርት፣ ራሳቸውም ታማኝ ከሆኑ ሰዎች ምክርን ስንፈልግ እና ስንቀበል አንስትም።
በቤተመቅደስ ውስጥ አዘውትረን በማምለክ ከመሣት መጠበቅ እንችላለን። ይህ ዘላለማዊ አመለካከትን እንድንይዝ ይረዳናል እንዲሁም ከቃል ኪዳኑ መንገድ ሊለዩን ወይም ዞር ሊያደርጉን ከሚችሉ ተጽእኖዎች ይጠብቀናል።
የዚህ የአስር ደናግላን ምሳሌ አስፈላጊ ትምህርት ወንጌልን ስንቀበል፣ መንፈስ ቅዱስ ከእኛ ጋር እንዲሆን ስንፈልግ እና ከመሳት ስንጠበቅ ልባሞች እንሆናለን የሚል ነው። አምስቱ ልባም ደናግላን ዘይት የሌላቸውን መርዳት እንዳልቻሉት ሁሉ ማንም ሰው በእኛ ፈንታ ወንጌልን ሊቀበል፣ መንፈስ ቅዱስን እንደ መሪ ሊወስድ እና ከመሳት ሊጠብቀን አይችልም። ይህንን ራሳችን ማድረግ አለብን።
ቀጥሎም አዳኙ የመክሊቶቹን ምሳሌ ተናገረ። በዚህ ምሳሌ፣ አንድ ሰው መክሊት ተብሎ የሚጠራን የተለያየ መጠን ያለው ገንዘብ ለሦስት አገልጋዮች ይሰጣል። ለአንዱ አምስት መክሊት፣ ለአንዱ ሁለት፣ ለሦስተኛው ደግሞ አንድ ይሰጣል። በጊዜ ሂደት፣ የመጀመሪያዎቹ ሁለት አገልጋዮች የተቀበሉትን በእጥፍ አሳደጉ። ሦስተኛው አገልጋይ ግን አንዷን መክሊት ወስዶ ቀበረ። መክሊታቸውን እጥፍ ላደረጉት ለሁለቱም አገልጋዮች ሰውዬው ለእያንዳንዳቸው፡-“መልካም፥ አንተ በጎ ታማኝም ባሪያ፤ በጥቂቱ ታምነሃል፥ በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ” ይላቸዋል።
ከዚያም መክሊቱን የቀበረውን አገልጋይ “ክፉ እና ሃኬተኛ” በማለት ይናገረዋል።” የዚህ አገልጋይ መክሊት ተወሰደበትና ተባረረ። ሆኖም፣ ይህ አገልጋይ መክሊቱን እጥፍ አድርጎ ቢሆን ኖሮ፣ ልክ እንደሌሎቹ አገልጋዮች ምስጋናንና ሽልማትን ባገኘ ነበር።
የዚህ ምሳሌ አንዱ መልእክት እግዚአብሔር የተሰጠንን ችሎታ እንድናጎላ ይጠብቅብናል፣ ነገር ግን እርሱ አቅማችንን ከሌሎች ጋር እንድናነጻጽር አይፈልግም። የ18ኛው መቶ ዘመን የአኒፖል የሃሲዲክ ምሁር ዙስያ ያቀረበውን ይህን መረዳት ተመልከቱ። ዙስያ የሚሞትበት ጊዜ እየቀረበ ሲመጣ መፍራት የጀመረ ታዋቂ አሰተማሪ ነበር። ደቀ መዛሙርቱም፣ “መምህር ሆይ፣ ለምን ትፈራለህ? ጥሩ ሕይወት ኖረሃል፣ በእርግጥ እግዚአብሄር ታላቅ ሽልማት ይሰጥሃል” አሉት።
ዙስያ እንዲህ አለ:- “እግዚአብሔር ‘ዙሲያ፣ ለምን ሌላኛው ሙሴ አልሆንክም?’ ቢለኝ ‘ለሙሴ የሰጠኸውን ታላቅ ነፍስን ስላልሰጠኸኝ ነው’ እለዋለሁ። በእግዚአብሔር ፊት ብቆም እርሱም ደግሞ፦ ዙሲያ፡ ለምን ሌላኛው ሰሎሞን አልሆንክም? ቢለኝ ‘የሰለሞንን ጥበብ ስላልሰጠኸኝ ነው’ እለዋለሁ። ነገር ግን በፈጣሪዬ ፊት ብቆምና ‘ዙስያ፣ ለምን ዙስያን አልሆንክም? እንድትሆን አቅም የሰጠሁህን ሰው ለምን አልሆንክም?’ ቢለኝስ በዚያ ምክንያት ነው የምፈራው” አላቸው።
በእርግጥ፣ ከእግዚአብሔር የተቀበልናቸውን ችሎታዎች ለማጉላት በአዳኙ ጥበብ፣ ምህረት እና ጸጋ ካልተደገፍን እግዚአብሔር ያዝንብናል። በእርሱ የፍቅር እርዳታ፣ የራሳችን ምርጥ ስሪት መሆን እንድንችል ከእኛ ይጠብቃል። በተለያዩ ችሎታዎች መጀመራችን ለእርሱ ምንም ማለት አይደለም። ለእኛም እንደዚያው መሆን አለበት።
በመጨረሻም፣ አዳኙ የበጎችን እና የፍየሎችን ምሳሌ ይናገራል። በክብሩ ሲመለስ “አሕዛብም ሁሉ በፊቱ ይሰበሰባሉ፤ እረኛም በጎቹን ከፍየሎች እንደሚለይ እርስ በርሳቸው ይለያቸዋል፥ በጎችን በቀኙ ፍየሎችንም በግራው ያቆማቸዋል።”
በቀኙ ያሉት በመንግሥቱ ወራሾች ሲሆኑ በግራው ያሉት ግን ርስት ሳያገኙ ቀሩ። የለያቸው ባህሪ ሲራብ ማብላታቸው፣ ሲጠማ ማጠጣታቸው፣ እንግዳ ሳለ ወደ ቤታቸው መቀበላቸው፣ ራቁቱን ሳለ ማልበሳቸው እና ሲታመም ወይም ሲታሰር መጠየቃቸው ወይም ይህን ሳያደርጉ መቅረታቸው ነበር።
በቀኝ እጅ እናም በግራ እጅ ያሉት ሁሉ ግራ ተጋብተው ነበር። ምግብ፣ የሚጠጣ ነገር እና ልብስ መቼ እንደሰጡት ወይም ተቸግሮ በነበረ ጊዜ መቼ እንደረዱት ወይም ይህን ሳያደርጉ እንደቀሩ ጠየቁ። አዳኙ “ከሁሉ ከሚያንሱ ከእነዚህ ወንድሞቼ ለአንዱ እንኳ ስላደረጋችሁት ለእኔ አደረጋችሁት” በማለት መለሠላቸው።
የምሳሌው መልዕክት ግልጽ ነው፡- ሌሎችን ስናገለግል፣ እግዚአብሔርን እናገለግላለን፤ ይህን ካላደረግን፣ እናሳዝነዋለን። የሰማይ አባትን ልጆች ህይወት ለመባረክ ስጦታችንን፣ ተሰጥኦችንን እና ችሎታችንን እንድንጠቀም ይፈልጋል። ሌሎችን ለማገልገል ያለው መለኮታዊ ግፊት በፊንላንዳዊው ገጣሚ በጆሃን ሉድቪግ ሩንበርግ በ19ኛው መቶ ዘመን በተጻፈው ድንቅ ግጥም ላይ ተገልጿል። እኔና ወንድሞቼ እና እህቶቼ በልጅነታችን ጊዜ ሁሉ “ገበሬ ፓቮ” የተሰኘውን ግጥም ደጋግመን ሰምተናል። በግጥሙ ውስጥ ፓቮ ከሚስቱ እና ከልጆቹ ጋር በማዕከላዊ ፊንላንድ ሀይቅ አካባቢ ይኖር የነበረ ድሃ ገበሬ ነበር። በፀደይ በረዶ መቅለጥ፣ በበጋ በረዶ ወይም በመጸው መጀመሪያ ላይ በመጣው ውርጭ ምክንያት በተከታታይ ለብዙ ዓመታት አብዛኛው ሰብሎቹ ይወድማሉ። አነስተኛው ምርት በገባ ቁጥር የገበሬው ሚስት “ፓቮ፣ ፓቮ፣ አንተ ያልታደልክ ሽማግሌ፣ እግዚአብሔር ትቶናል” ስትል በምሬት ትናገር ነበር። ፓቮ በተራው በቁጣ እንዲህ ይላል፡- “ህፃናቱ እንዳይራቡ ዳቦ ለመስራት የግንድ ቅርፊትን ከአጃው ዱቄት ጋር ቀላቅዪ። ረግረጋማ ቦታዎችን ለማፍሰስ ጠንክሬ እሰራለሁ። እግዚአብሔር እየፈተነን ነው፣ እርሱ ግን ያዘጋጃል።”
አዝመራው በጠፋ ቁጥር ፓቮ ረሃብን ለመከላከል በዱቄት ውስጥ የተቀላቀለውን የግንድ ቅርፊት በእጥፍ እንድትጨምር ለሚስቱ መመሪያ ይሰጥ ነበር። እንዲሁም የመሬቱን ውሃ ለማፍሰስ እና የእርሻ መሬቶቹን ለበልግ ፍሳሽ እና ለበልግ መጀመሪያ ውርጭ ተጋላጭነትን ለመቀነስ ጉድጓዶችን በመቆፈር ጠንክሮ ሰራ።
ከአመታት ችግር በኋላ ፓቮ በመጨረሻ የበለጸገ ሰብል ሰበሰበ። ሚስቱ በጣም ተደሰተች፣ “ፓቮ፣ ፓቮ፣ እነዚህ አስደሳች ጊዜያት ናቸው! የዛፍ ቅርፊትን የምንጥልበት እና በአጃ ብቻ የተሰራ ዳቦ የምንጋግርበት ጊዜ አሁን ነው።” ነገር ግን ፓቮ የሚስቱን እጅ ያዘና፣ “የጎረቤታችን ማሳ ደርቆአልና ግማሹን ዱቄት ከግንድ ቅርፊት ጋር ቀላቅዪ” አላት። ፓቮ የተጎዳውን እና የተቸገረውን ጎረቤቱን ለመርዳት የእሱን እና የቤተሰቡን ችሮታ ሠዋ።
የአዳኙ የበጎች እና የፍየሎች ምሳሌ ትምህርት የተሰጡንን ስጦታዎች—ጊዜን፣ ችሎታዎችን እና በረከቶችን—የሰማይ አባትን ልጆች በተለይም በጣም ተጋላጭ የሆኑትን እና የተቸገሩትን ለማገልገል መጠቀም እንዳለብን ነው።
ቀደም ብዬ ለጠቀስኩት ለተጨነቀችው የመጀመሪያ ክፍል ልጅ እና ለእያንዳንዳችሁ ግብዣዬ ኢየሱስ ክርስቶስን እንድትከተሉ እና ውድ ጓደኛችሁን እንደምታምኑ ሁሉ መንፈስ ቅዱስን እንድታምኑ ነው። በሚወዷችሁ እንዲሁም አዳኙን በሚወዱ ላይ ተደገፉ። ልዩ ችሎታችሁን ለማዳበር እና ቀላል ባይሆንም፣ ሌሎችን ለመርዳት የእግዚአብሔርን መመሪያ ፈልጉ። ከአዳኙ ጋር ለመገናኘት ዝግጁ ትሆናላችሁ እንዲሁም ፕሬዘዳንት ኔልሰንን በደስታ እና ተስፋ በማድረግ መቀላቀል ትችላላችሁ። ይህን በማድረግ፣ ዓለምን ለኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም ምጽአት በማዘጋጀት ትረዳላችሁ እንዲሁም ወደ ጌታ እረፍት ለመግባት አሁን እና ወደፊት በበቂ ተስፋ ትባረካላችሁ።
ከአዲስ መዝሙራችን በአንዱ ላይ እንዲህ እንዘምራለን፡
በኢየሱስ ክርስቶስ ስም፣ አሜን።