ንስሐችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ሸክም አይሆንም፤ ደስታውን ብሩህ ያደርግለታል።
ንስሃ ለመግባት የሚቀርብ ግብዣ የእግዚአብሔር ፍቅር መገለጫ ነው። ለዚያ ግብዣ ይሁንታን ማሣየት የኛ መገለጫ ነው።
ከበርካታ አመታት በፊት ወደ ፍሎሪዳ በሄድኩበት ወቅት መጽሐፍ እያነበብኩ ውጭ ተቀምጬ ነበር። ርዕሱ ምንም እንኳን አሁን ፍፁም ባንሆንም አሁንም ወደ መንግሥተ ሰማያት መግባት እንደምንችል ይጠቁም ነበር። በአጠገቤ እያለፈች የነበረች ሴት፣ “የሚቻል ይመስልሻል?” ስትል ጠየቀችኝ።
ግራ ተጋብቼ ቀና ብዬ ተመለከትኳት ከዚያም እያነበብኩት ስለነበረው መጽሃፍ እያወራች እንደሆነ ተገነዘብኩኝ። ይህን የመሠለ አስቂኝ ነገር ተናገርኩ፣ “ደህና፣ እኔ ያን ያህል ዘልቄ አላነበብኩትም፣ ሆኖም ፍፃሜው ምን እንደሚሆን አሳውቅሻለሁ።”
ውይ በጊዜ ወደ ኋላ መጓዝ ብችል ምንኛ እመኛለሁ! እንዲህ እላት ነበር፣ “አዎ፣ ይቻላል! ምክንያቱም መንግሥተ ሰማያት ፍጹም ሆነው ለኖሩ ሠዎች አይደለችም፤ እርሷ ይቅር ለተባሉ፣ ክርስቶስን ደጋግመው ለሚመርጡ ሰዎች ናት።”
ዛሬ፣ አንዳንድ ጊዜ “ንስሐና ይቅርታ ከእኛ በቀር ለሁሉም የሚሠሩ ለሚመሥለን” ሠዎች መናገር እፈልጋለሁ። “ተመሳሳይ ስሕተቶችን መሥራቴን ስለቀጠልኩኝ፣ ምናልባት እኔ በቃ እንዲህ ነኝ” ብለው በድብቅ ለሚጨነቁት። እንደ እኔ የቃል ኪዳኑ መንገድ በጣም አቀበት እንደሆነ ተሠምቷቸው ለሚያውቁ ሠዎች ቃል ኪዳን የአቀበት ጉዞ ነው ማለት ይቻላል።
ከፊጂ የመጣ ሽማግሌ ጋንጋህ የሚባል በአውስትራሊያ የሚኖር ድንቅ ሚስዮናዊ፣ በሽኝት ምስክርነቱ ላይ የሚሠማውን ተመሳሳይ ስሜት አካፍሏል፦ “እግዚአብሔር እንደሚወደኝ አውቃለሁ፣ ሆኖም አንዳንድ ጊዜ፣ እግዚአብሔር እንደምወደው ያውቃል? ስል አስባለሁ። ምክንያቱም ፍፁም አይደለሁም፣ እንዲሁም አሁንም ሥህተት እሠራለሁ”
በዚያ በአንድ በእውነተኛ ሥሜት በተጠየቀ ውል እያለ ለሚመጣ ጥያቄ ሽማግሌ ጋንጋህ ብዙ ጊዜ የሚያስጨንቀኝን ነገር በትክክል ጠቅለል አድርጎ አቅርቧል። ምናልባት እናንተም፣ “በጣም እየሞከርኩ ነው፣ ግን በእውነት እንደምሞክር እግዚአብሔር ያውቃል? በማለት እያሰባችሁ ይሆናል። መሥፈርቶችን ማሟላት ሳልችል ስቀር፣ እግዚአብሄር አሁንም እንደምወደው ያውቃል?”
ይህንን ስቀበል በጣም አዝናለሁ፣ ሆኖም እኔም እራሴ ከአዳኙ ጋር ያለኝን ግንኙነት የምለካው በፍፅምና በምኖርበት መንገድ ነበር። የታዛዥነት ሕይወት ማለት ፈጽሞ ንስሐ መግባት አያስፈልገኝም ማለት እንደሆነ አስቤ ነበር። እናም በየዕለቱ ስህተት ስሰራ “በእኔ በጣም ተበሣጭቶ መሆን አለበት” ብዬ በማሰብ ራሴን ከእግዚአብሔር አራቅኩኝ።
ያ እውነት አይደለም።
ወደ አዳኙ ለመሄድ በበቂ ሁኔታ ንፁህ እስክትሆኑ ወይም ፍፁም እስክትሆኑ ድረስ ከጠበቃችሁ ቁም ነገሩ እንዳለ እንዳልገባችሁ አውቂያለሁ።
ስለትእዛዛት እና ስለታዛዥነት በተለየ መንገድ ብናስብስ?
እግዚአብሔር ስህተት ሥንሰራ ቢጨነቅም፣ ከተሳሳትን በኋላ ለሚሆነው ነገር ይበልጥ እንደሚጨነቅ እመሠክራለሁ። አሁንም አሁንም ወደ እሱ ፊታችንን ልንመልስ ነው? በዚህ የቃልኪዳን መንገድ ውስጥ ልንቆይ ነው?
ምናልባት “ብትወዱኝ ትዕዛዜን ጠብቁ” የሚለውን የጌታ ቃል ሰምታችሁ ይሆናል ከዚያም ሁሉንም ትዕዛዛት ባለመጠበቃችሁ የተሥፋ መቁረጥ ተሰምቷችሁ ይሆናል። ንስሀ መግባትም ትዕዛዝ እንደሆነ ላስታውሣችሁ! እንደ እውነቱ ከሆነ በቅዱሣት መጻሕፍት ውስጥ በጣም የተደጋገመው ትዕዛዝ እሱ ሊሆን ይችላል።
አልማ በብቸኝነት፣ “ንሥሐን እናገር ዘንድ ምነው መልአክ በሆንኩና [የልቤ] መሻት በሞላልኝ፣” ባለ ጊዜ ስህተቶቻችንን በመጠቆም ሊያሳፍረን እየሞከረ አልነበረም። ንስሃ እንድንገባ የፈለገው እኔ እና እናንተ ከምድሪቱ ገፅ ላይ ሃዘንን ማስወገድ እንድንችል ነው። አልማ ኃጢአትን የጠላበት አንዱ ምክንያት ህመም ስለሚያስከትልብን ነው።
አንዳንድ ጊዜ፣ ልክ በግንባሬ ላይ እንደተለጠፈ የማስታወሻ ወረቀት ትዕዛዛቱ ከህመም የሚያርቁ መንገዶች እንደሆኑ ማስታወስ አለብኝ። ንስሐም እንዲሁ። ነቢያችን፣ “አዳኙ ሁልጊዜ ይወደናል በተለይ ንስሐ ስንገባ”በማለት ተናግረዋል።
ስለዚህ ጌታ፣ “ንስሐ ግቡ፣ ንስሐ ግቡ” ፣ “እወዳችኋለሁ ሲል አስቡት። እወዳችኋለሁ” ህመም የሚያስከትልባችሁን ባህሪ ትታችሁ ከጨለማ እንድትወጡ እና ወደ ብርሃኑ እንድትዞሩ በመጋበዝ ሲለምናችሁ አስቡ።
በሴት ልጄ በካርሊ አጥቢያ አንድ አዲስ ካህን ቅዱስ ቁርባንን ለመባረክ ተንበረከከና “የልጅህን ደም በማስታወስ ያደርጉት ዘንድ” ከማለት ይልቅ ሳያውቅ፣ “የልጅህን ፍቅር በማስታወስ ያደርጉት ዘንድ” አለ። የእነዚያ ቃላት እውነታ ወደ ውስጧ ሲዘልቅ የካርሊ አይኖች በእንባ ተሞሉ።
አዳኛችን ስለሚወዳችሁ የኃጢያት ክፍያው ያስከተለበትን ስቃይ ለመቀበል ፈቃደኛ ነበር። በርግጥ በተሠቃየ ጊዜ “በፊቱ [የነበረው] ደስታ” እናንተ ናችሁ።
ንስሃ ለመግባት የሚቀርብ ግብዣ የእግዚአብሔር ፍቅር መገለጫ ነው።
ለዚያ ግብዣ ይሁንታን ማሣየት የኛ መገለጫ ነው።
የምትወዱትን የክርስቶስ ምሥል በአዕምሯችሁ አምጡ። አሁን የእርሡን ስጦታ በተጠቀማችሁ ቁጥር በደስታ ብሩህ ፈገግታ ሲያሣይ አስቡት፣ ምክንያቱም እርሱ “ፍጹም የሆነ የተስፋ ብርሃን” ነው።
አዎ፣ ንስሐችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ሸክም አይሆንም፤ ደስታውን ብሩህ ያደርግለታል።
ያንን እናስተምር!
ምክንያቱም ንስሃ ከሁሉም የተሻለው ዜናችን ነውና!
ስህተት በፍፁም ባለመሥራት በቃል ኪዳኑ መንገድ ላይ አንቆይም። በመንገዱ ላይ የምንቆየው በየዕለቱ ንስሃ በመግባት ነው።
ንስሀ በምንገባበት ጊዜም፣ እግዚአብሔር ይቅር የሚለን ሳያሳፍረን፣ ከማንም ጋር ሳያወዳድረን ወይም በቁጣ ሳይነቅፈን፣ ይህ ባለፈው ሳምንት ንስሃ የገባችሁበት ተመሳሳይ ነገር ነው ሣይለን ነው።
በጉልበታችን ተንበርክከን ስንፀልይ እና ንስሐ ስንገባ ባየን ቁጥር ይደሰታል። በእርሱ ደስተኞች ስለሆንን እኛን ይቅር ማለት ያስደስተዋል።
ያ እውነት እንደሆነ አይሠማችሁም?
ታዲያ ለማመን የከበደን ለምንድን ነው?!
ታላቁ ከሳሽ እና አታላይ ሰይጣን ሃፍረትን ተጠቅሞ ከእግዚአብሔር ያርቀናል። ኃፍረት በጣም ከባድ የሆነ ጨለማ ነው ከሰውነትህ ብትወስደው እውነተኛ ክብደት ወይም ክብደት ይኖረዋል.
“ምን እያሰባችሁ ነበር?” እያለ የሚወቅሣችሁ ድምጽ ሃፍረት ነው። “አንድ ነገር በትክክል መሥራት ትችላላችሁ?”
ሃፍረት የሚነግረን ስህተት እንደሠራን ሣይሆን እኛው እራሣችን ስህተቶች እንደሆንን ነው። “ተደበቁ” የሚለውን ድምፅ ልትሰሙም ትችላላችሁ። ጠላት ዋጋው በጣም ከፍተኛ ስለሆነ ያለውን ተስፋ ሁሉ በማስወገድ ይህ በጨለማ ውስጥ ቢቆይ የተሻለ እንደሚሆን በመንገር የሃፍረት ሥሜታዊ ጫና እዚያው እንዲቆይ የተቻለውን ሁሉ ያደርጋል።
ሰይጣን የተስፋችን ሌባ ነው።
ይህንን መስማት ያስፈልጋችኋል፤ ስለዚህ እነዚህን ቃላት ድምፄን ከፍ አድርጌ እናገራለሁ፦ እናንተ በጭንቅላታችሁ ውስጥ የሚሠማው ድምጽ ወይም የፈፀማችኋቸው ስህተቶች አይደላችሁም። እናንተም ያንን ጮክ ብላችሁ መናገር ያስፈልጋችሁ ይሆናል። ሰይጣንን “ለዛሬ አልተሣካልህም” በሉት። ወደ ኋላህ እርሡት።
ያ ወደ አዳኛችሁ የሚመልሣችሁ አምላካዊ ሀዘን ይሠማችሁ ከዚያም የእርሱ ፀጋ ወደ እናንተ እና ወደምትወዷቸው ሰዎች ህይወት ውስጥ ሲገባ ተመልከቱ። የተሰበረ ልብን በድፍረት ወደ እርሱ ባቀረብንበት ደቂቃ፣ ወዲያውኑ እዚያ እንደሚገኝ ቃል እገባለሁ።
አንድ ሰው በመስመጥ ላይ እንደሆነ ብታዩ እጃችሁን ዘርግታችሁ አታድኑትም? አዳኛችሁ የተዘረጉትን እጆቻችሁን እንደማይቀበል ልትገምቱ ትችላላችሁ? በርግጥ ንፁህ ዓየር እንወስድ ዘንድ እኛን ለማንሳት ወደ ውሃው ውስጥ ጠልቆ ከነገሮች ሁሉ በታች እንደሚወርድ አስባለሁ! የክርስቶስ ብርሃን ከሚፈነጥቀው ማንም ዝቅ ብሎ ሊወርድ አይችልም።
አዳኙ ለዘለዓለም ከሃፍረት ጨለማ የበለጠ ብሩህ ነው። መቼም ዋጋ ቢስ እንደሆናችሁ እንዲሠማችሁ አያደርግም። ስለዚህ በቅርበት ተመልከቱ።
-
ይህ እጅ ዋጋን ይወክላል ብላችሁ አስቡ።
-
ይህ እጅ ታዛዥነትን ይወክላል። ምናልባት ዛሬ ጠዋት ከእንቅልፋችሁ ተነስታችሁ ትርጉም ያለው ጸሎት አድርጋችሁ እንዲሁም የእግዚአብሔርን ድምፅ ለመስማት ቅዱሳት መጻህፍትን አንብባችሁ ይሆናል። ጥሩ ውሳኔዎችን አድርጋችኋል እንዲሁም በዙሪያችሁ ያሉትን ሠዎች የክርስቶስን በሚመስል መንገድ እየያዛችኋቸው ነው። አጠቃላይ ጉባኤን እያዳመጣችሁ ነው! ታዛዥነታችሁ እየታየ ነው!
-
ወይም ምናልባት ነገሮች እንደተጠበቁት በደንብ አልሆኑም። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከሰማይ ጋር ለመገናኘት እነዚያን ትናንሽ እና ቀላል ነገሮች ለማድረግ እየተቸገራችሁ ነው። ሃፍረት እንዲሠማችሁ ያደረገ ነገርን አድርጋችኋል።
-
ዋጋችሁ የታለ? ይህ እጅ ጭራሹን ተንቀሳቅሷል?
ዋጋችሁ ከመታዘዝ ጋር የተያያዘ አይደለም። ዋጋችሁ ቋሚ ነው፤ መቼም አይለወጥም። የተሰጣችሁ በእግዚአብሔር ሲሆን እናንተ ወይም ሌላ ሰው እሱን ለመለወጥ ምንም ማድረግ አትችሉም። መታዘዝ በረከት ያመጣል፤ ያ እውነት ነው። ዋጋ ከነሡ ውስጥ አይገኝም። ውሳኔያችሁ የትም ቢያደርሣችሁ ሁልጊዜም ዋጋችሁ “በእግዚአብሔር ፊት ታላቅ” ነው።
ስሕተቶችን በምሠራበት ጊዜ ከክርስቶስ ጋር በቃል ኪዳን ግንኙነት ውስጥ መቆየት እፈልጋለሁ፤ ለምን እንደሆነ እነግራችኋለሁ።
የዳይቪንግ ሥልጠና እየወሰድኩ ነው ያደግኩት እናም ዳኞች ለአንድ ዳይቭ ውጤት ሲሠጡ አፈፃፀሙን እንደሚመለከቱ ተማርኩ። ዳይቭ አደራረጉ ፍፁም ቀጥ ያለ ነበር፣ የእግር ጣቶች ወደ ላይ ቀጥ ብለው ነበር እንዲሁም የተረጨው ውሃ ትንሽ ነበር? ከዚያም አንድ ፍፁም የተለየ ነገር ያደርጋሉ። የአስቸጋሪነቱን ደረጃ ያመለክታሉ።
ሁሉም የአስቸጋሪነቱን ደረጃ ያመለክታሉ። እየጠለቃችሁበት ያለውን ችግር በእውነት የሚያውቀው አዳኛችሁ ብቻ ነው። ግንኙነት እንዲኖረኝ የምፈልገው ከሚረዳኝ፣ ልቤን ከሚያውቅ እና ምን ያህል እየሞከርኩ እንደሆነ ከሚያውቅ ሠው ጋር ነው!
የጨለማው ጭጋግ በሁላችንም በመንገደኞች ላይ እየወረደመሆኑን፣ጉዟችን በቆሻሻ ወንዝ በኩል እንደሆነያውቃል፣ስለዚህ የብረት ዘንግ ብንይዝምእንኳን ይረጭብናል።
ወደ ክርስቶስ መምጣት ማለት ሁል ጊዜ እጆቹ ወደ እናንተ እንደተዘረጉ በተገለጠ የተረጋገጠ ተስፋ “ትረዳኛለህ?” ብሎ መጠየቅ ማለት ነው። ይህ አዲስ የንስሃ እይታ ምንም እንኳን አሁን ፍጹም የሆነ ታዛዥነት ባይኖረንም እርሡን ስለምንወደው በፍቅር ለመታዘዝ፣ ደግመን ደጋግመን ለመቆየት መምረጥን እንሞክራለን ማለት እንደሆነ አምናለሁ
የንጉሥ ቢኒያም ህዝቦች ያለማቋረጥ መልካምን መሥራት እንጂ ከእንግዲህ ሃጥያት ለመፈጸም ምንም ፍላጎት እንዳልነበራቸው ታስታውሣላችሁ? ድንኳናቸውን ጠቅልለው ወደ ቤታቸው የሄዱ እና ከዚያ በኋላ ሌላ ሥህተት ያልሠሩ ይመስላችኋል? በጭራሽ። ልዩነቱ ሃጢአት መሥራት አለመፈለጋቸው ነው። በፍቅር ይታዘዙ ነበር! ልባቸው በእግዚአብሔር ላይ ትኩረት አደረገ እንዲሁም ተደገፈ!
በአንድ ወቅት በባህር ዳርቻ ላይ አንድ ወፍ ክንፎቹን በሃይል እያማታች ራሷን መቆጣጠር ባለመቻል እየተወዛወዘች ወደ ነፋሱ አቅጣጫ ስትበር ሆኖም እዚያው ቦታ ላይ ቆማ አየሁ። በኋላም ከዚያ ከፍ ብሎ የሚበር ሌላ ወፍ አስተዋልኩ። ወደላይ እየተነሣ እና ስለነፋሱ ግድ ሣይሰጠው በቀላሉ እየተንሳፈፈ ነበር። ያ በራሳችን ለማድረግ በመሞከር እና “በክን[ፎቹ] ፈውስ” እንዲያነሳን በመፍቀድ ወደ አዳኛችን በመመለስ መካከል ያለው ልዩነት ነው።
በአውስትራሊያ የሚሲዮን መሪዎች እያለን እያንዳንዱን ሚስዮናዊ ለመጨረሻ ጊዜ በጎበኘን ጊዜ ሰዎቹ ለአዳኙ ቅርብ በሆኑበት ለእነሱ ሲጸልይ መስማት እንደቻሉ ተነጋገርን።3 ኔፊ 17 “አዳኙ ስለእናንተ ሲጸልይ ብትሰሙ ምን የሚል ይመስላችኋል?” ብለን ጠየቅናቸው።
የእነሱን መልሶች መስማት በሕይወቴ ከነበሩኝ እጅግ በጣም መንፈሳዊ የሆኑ ተሞክሮዎች አንዱ ነበር። “አዳኛችሁ እያጋጠማችሁ ያለውን የችግር ደረጃ ያውቃል። እርሱ ተሰምቶታል” ብለን ስናስታውሳቸው ሁሉም ሚስዮናውያን ቆም ይሉና እንባ በዓይኖቻቸው ይሞላ ነበር።
እነዚያ ሚስዮናውያን በጸጥታ እና በርኅራኄ ያካፈሉት ይህንን ነበር፦ “ኢየሱስ ለአብ፣ አቅሟ የቻለውን እያደረገች ነው። ምን ያህል ጥረት እያደረገች እንደሆነ አውቃለሁ ብሎ ይነግረዋል።” ሌላው ደግሞ እንዲህ አለ፣ “በህይወቱ ውስጥ ምንም ነገር ቢከሠትም በጣም እኮራበታለሁ።”
ይህንን እንሞክር። ዛሬ ማታ ፀሎት ከመጸለያችሁ በፊት ኢየሱስ ክርስቶስ በቅርባችሁ እንዳለ አስቡ። እርሡ ከአባት ጋር አማላጃችን ነው። እራሳችሁን እንዲህ ብላችሁ ጠይቁ፣ “አዳኙ ስለ እኔ ምን ይላል?”
ከዚያም ፀጥ በሉ።
ስለእናንተ መልካም ነገር የሚናገረውን ምርጥ ጓደኛችሁ የሆነውን የአዳኙን እና በእውን ያለውን የሠማይ አባታችሁን ድምጽ አዳምጡ። ምንም ቢሆን ፍቅራቸው እና የእናንተ ዋጋ ሁሌም ታላቅ እንደሆነ አስታውሱ።
ኢየሱስ ክርስቶስ በጨለማ ለለሚሄዱት ብርሃን እንደሚሰጥ ለመመስከር እዚህ ቆሜያለሁ። ያ ድምፅ እንድትደበቁ እየነገራችሁ እንደሆነ በሚሠማችሁ በእነዚያ ቀናት በጨለማ ክፍል ውስጥ ብቻችሁን መደበቅ እንዳለባችሁ በሚነግራችሁ ጊዜ ደፋር እንድትሆኑ እና ክርስቶስን እንድታምኑ እጋብዛችኋለሁ! ፍፁም ብሩህ ተስፋችን ወደሆነው ራመድ በሉና መብራቱን አብሩት።
የእርሡ ብርሃን ስለበራ ዙሪያችሁን ብቸኝነት የተሰማቸውን ሰዎች ታያላችሁ፣ አሁን ግን ብርሃኑ ስለበራ፣ እናንተ እና እነሱ “በጨለማ ውስጥ ሣለን የፈራነው ለምንድን ነው? ያን ያህል በዚያ የቆየነውስ ለምንድን ነው?” በማለት ትገረማላችሁ።
“የብርሃናት ሁሉ ጌታ በእጆቹ ይቀፋችሁ እንዲሁም ያጽናናችሁ ያለማቋረጥም ይውደዳችሁ።” እንውደደው እንዲሁም ደግመን ደጋግመን እንምረጠው። በኢየሱስ ክርስቶስ ስም፣ አሜን።