አጠቃላይ ጉባኤ
ራስን በመግዛት ባህርይ ተጎናጽፎ
የጥቅምት 2025 (እ.አ.አ) አጠቃላይ ጉባኤ


15:8

ራስን በመግዛት ባህርይ ተጎናጽፎ

ሁላችንም አእምሯችንንና ልባችንን በክርስቶስ ዓይነት የራስን በመግዛት ባሕርይ እንድናጌጥ አጥብቄ እጋብዛችኋለሁ።

ፕሬዚዳንት ራስል ኤም. ኔልሰን በግንቦት 2021 (እ.አ.አ) የሶልት ሌክን ቤተመቅደስ የእድሳት ስራን በጎበኙበት ወቅት፣ በተወሰነ ሀብትና በማያወላውል እምነት የጊዜን ፈተና ተቋቁሞ የኖረውን እና ስጋዊ እና መንፈሳዊ ድንቅ ስራ የሆነውን ቅዱስ ህንጻ ለመገንባት መስራቾች የነበራቸውን ጥረት አድንቀዋል። ይሁን እንጂ ከጊዜ በኋላ በቤተመቅደሱ የመጀመሪያ የመሰረት ድንጋዮች ላይ ክፍተቶችን እንዲሁም በግንባታው ውስጥ አለመረጋጋትን ያስከተለውን የመሸርሸር ውጤቶችንም አስመልክተዋል፣ ይህም ለግንባታ ማጠናከሪያ አስፈላጊነት ግልጽ ምልክቶች ነበሩ።

ፕሬዚዳንት ኔልሰን ከሶልት ሌክ ቤተመቅደስ ውጭ።

ከዚያም የተወደዱት ነቢያችን የቤተመቅደሱን የተፈጥሮ ኃይሎችን ለመቋቋም ዋና ዋና እርምጃዎች መተግበር እንደሚያስፈልግ፣ በኢየሱስ ክርስቶስ ውስጥ የራሳችንን መንፈሳዊ መሠረት ለማጠናከር፣ ምናልባትም ከዚህ በፊት ወስደን የማናውቅ እርምጃዎችን መውሰድ እንዳለብን አስተምረውናል። በማይረሳው መልእክታቸው፣ በግል እንድናሰላስል ሁለት ጥልቅ ጥያቄዎችን ትተውልናል፦ “የእናንተ መሠረት ምን ያህል ጠንካራ ነው? እንዲሁም ለወንጌል ምስክርነታችሁ እና መረዳታችሁ ምን ዓይነት ማጠናከሪያዎች ያስፈልጋቸኋል?”

የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል በመንፈሳችን ውስጥ የሚከሰተውን መንፈሳዊ ውድቀት ለመከላከል፣ መሠረታችንን በኃይል ለማጠናከር እና በእምነታችን ውስጥ ክፍተቶችን እና በምስክርነታችን እንዲሁም በቅዱስ የወንጌል እውነቶች ግንዛቤ ውስጥ አለመረጋጋትን ለማስወገድ መለኮታዊ ምሪት ይሰጠናል። ይህንን ዓላማ ለማሳካት በነቢዩ ጆሴፍ ስሚዝ አማካኝነት ለጆሴፍ ናይት የተሰጠ በተለይ ጠቃሚ የሆነ አንድ ራእይ በትምህርትና ቃል ኪዳኖች ክፍል 12 ውስጥ ይገኛል፣ እርሱም የጌታን ፈቃድ በቅንነት ለመረዳት የፈለገ ጻድቅ ሰው፣ ለውጡ ውጫዊ ብቻ ያልሆነ፣ ነገር ግን እንደ ሰማይ ምሰሶዎች በደቀ መዝሙርነቱ የማይናወጥ ሆኖ የቆመ ነበር። ጌታ እንዳወጀው፦

“እነሆ፣ ለአንተ እና እንዲሁም ይህንን ስራ ለመፈጸምና ለመመስረት ለሚሹ ሁሉ እናገራለሁ።

“በሀላፊነት እምነት በተጣሉበት ነገሮች ሁሉ ራሱን ገዝቶ፣ በእምነት፣ በተስፋና በለጋስነት፣ እናም እራሱን ትሁት በማድረግና በፍቅር ተሞልቶ ካልሆነ በቀር፣ ማንም ሰው በዚህ ስራ ውስጥ መርዳት አይችልም።”

በዚህ ቅዱስ መገለጥ ውስጥ ተመዝግቦ የሚገኘው የአዳኛችን መመሪያ፣ ራስን የመግዛት ባህርይ በኢየሱስ ክርስቶስ ውስጥ ለሚገኘው ጽኑ መሠረት አስፈላጊ ማጠናከሪያ መሆኑን ያስታውሰናል። ይህ ለአገልግሎት ለተጠሩት ብቻ ሳይሆን፣ ከጌታ ጋር ቅዱስ ቃል ኪዳን የገቡና እርሱን በታማኝነት ለመከተል ለተቀበሉት ሁሉ እጅግ አስፈላጊ ከሆኑት መልካም ባህርያት አንዱ ነው። ራስን መግዛት በዚህ ራእይ ውስጥ የተጠቀሱትን ሌሎች የክርስቶስን ባህርያት ማለትም ትህትናን፣ እምነትን፣ ተስፋን፣ ፍቅርን እንዲሁም ከእሱ የሚመነጨውን ንጹህ ፍቅርን ያስታጥቃል እንዲሁም ያጠናክረዋል። ከዚህም በላይ ራስን የመግዛት ባህርይ ማዳበር በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ያለንን መሠረት ሊያዳክሙ በሚችሉ ዓለማዊ ተጽዕኖዎች ምክንያት በሚመጣው ስውር ሆኖም የማያቋርጥ መንፈሳዊ ድካም ነፍሳችንን ለመጠበቅ የሚያስችል ጠቃሚ መንገድ ነው።

እውነተኛ የክርስቶስን ደቀ መዛሙርት ከሚያጌጡ ባህርያት መካከል ራስን መግዛት የአዳኙን ማንነት የሚያንጸባርቅ ሲሆን ለመለኰታዊ ተጽዕኖ እራሳቸውን ክፍት ላረጉ ሁሉ የሚገኝ ውድ የመንፈስ ፍሬ ነው። በጎነት ምኞቶችን እና ስሜቶችን በጥበብ እና በረጋ መንፈስ በመቅረጽ ለልብ መቻቻልን የሚያመጣ ነው። በቅዱሳን መጻህፍት ውስጥ፣ ራስን መግዛት በመንፈሳዊ ጉዟችን ውስጥ እድገት ለማድረግ ወሳኝ አካል እንደሆነ ተገልጿል፤ ይህም ስሜታችንን፣ ቃላችንንና ድርጊታችንን በማጥራት ትዕግሥትን፣ አምላካዊ ፍርሃትንና ርኅራሄን እንድናዳብር ያደርገናል።

የክርስቶስ ደቀ መዛሙርት ይህን የክርስቶስ ዓይነት ባህርይ ለማዳበር የሚጥሩ ከሆነ ይበልጥ ትሁትና አፍቃሪ ይሆናሉ። የቍጣ ነፋስ በኃይል በሚነፍስበት ጊዜም እንኳ፣ እነርሱም ቍጣቸውን ለመቈጣጠር፣ ትዕግሥትን ለማዳበርና ሌሎችን በትዕግሥት፣ በአክብሮትና ክብር ለመያዝ የሚችሉ ይሆናሉ። በየዋህነት እና በመንፈስ ቅዱስ በመመራት፣ በመንፈሳዊ ጥበብ ለመስራት እንጂ በግዴለሽነት ላለማድረግ ይጥራሉ። ሐዋርያው ጳውሎስ እንዳስተማረው በክርስቶስ አማካኝነት ሁሉንም ነገር ማድረግ እንደሚችሉ ስለሚያውቁ በዚህ መንገድ ለመንፈሳዊ መበስበስ ተጋላጭ ይሆናሉ፣ ይህም ስለ እርሱ የሚሰጡትን ምስክርነት ሊያናውጡ በሚችሉ ፈተናዎች ፊት እንኳን ያጠናክራቸዋል።

ጳውሎስ ለቲቶ በጻፈው ደብዳቤ ላይ አዳኙን ወክለው የእርሱን ፈቃድ በእምነትና በታማኝነት መፈጸም የሚፈልጉ ሰዎች ሊያሟሏቸው ስለሚገቡ ብቃቶች ቅዱስ ምክር ሰጥቷል። የእንግዳ ተቀባይነት፣ ጠንቃቃ፣ ጻድቅና የቅድስና ባህርያት ሊኖራቸው እንደሚገባ ተናግሯል፤ እነዚህ ባህርያት ደግሞ ራስን የመግዛት ባህርይን በግልጽ የሚያንፀባርቁ ናቸው።

ጳውሎስ፣ እነርሱ “የማይኮራ፥ የማይቆጣ፥ … [እና] የማይጨቃጨቅ” መሆን እንዳለባቸው አሳስቧቸዋል። እንዲህ ያሉት ባህርያት ከአዳኙ አስተሳሰብ ጋር የሚቃረኑና እውነተኛ መንፈሳዊ እድገት እንዳይኖር ዕንቅፋት የሚሆኑ ናቸው። በቅዱሳን መጻህፍት ውስጥ “የማይኮራ” ተብሎ የተተረጐመው ቃል አንድ ሰው በትዕቢት ወይም በኵራት እርምጃ ለመውሰድ ፈቃደኛ አለመሆኑን ያመለክታል፤ “የማይቆጣ” ትዕግሥት የማጣት እና የመበሳጨት ተፈጥሯዊ ፍላጐትን የሚከላከል ሰው ነው፤ እንዲሁም “የማይጨቃጨቅ” ጠበኛነትን እና ጨካኝ ባህሪን በቃል፣ በአካል እና በስሜታዊነት የሚቃወም ሰው ነው። ባህርያችንን በእምነትና በትህትና ለመለወጥ ስንጥር፣ በጸጋው ጠንካራ ዓለት ላይ በጽኑ መቆም እንችላለን እንዲሁም በቅዱስ እጆቹ ውስጥ ንጹህና የተጣራ መሣሪያ መሆን እንችላለን።

ሐና እና ሳሙኤል

ራስን የመግዛት ባህርይ ማዳበር አስፈላጊ ስለመሆኑ ሳሰላስል፣ የነቢዩ ሳሙኤል እናት የሆነችው ሐና የተናገረችው ነገር ትዝ ይለኛል፤ ሐና ከባድ ፈተናዎች ቢያጋጥሟትም እንኳ ለጌታ የምስጋና መዝሙር የዘመረች አስደናቂ እምነት ያላት ሴት ነበረች። እርሷም እንዲህ አለች፦ “አትታበዩ፥ በኩራትም አትናገሩ፤ እግዚአብሔር አዋቂ ነውና፥ እግዚአብሔርም ሥራውን የሚመዝን ነውና፥ ከአፋችሁ የኵራት ነገር አይውጣ።” ዝማሬዋ ከጸሎት በላይ ነው—ይህም በትህትና፣ ራስን በመቆጣጠር እና በመጠን እርምጃ ለመውሰድ ከውስጥ የሆነ ግብዣ ነው። ሐና እውነተኛ መንፈሳዊ ጥንካሬ የሚገለጸው በድንገተኛ ምላሽ ወይም በትዕቢተኛ ቃላት ሳይሆን ከጌታ ጥበብ ጋር በሚስማማ ሚዛናዊና ዐሳቢ አመለካከት መሆኑን እንድናስታውስ ታደርገናለች።

ብዙ ጊዜ ዓለም ጠበኛነትን፣ እብሪተኝነትን፣ ትዕግስት ማጣትና ከልክ ያለፈ ርኵሰት የሚንጸባረቅባቸውን ባህርያት ከፍ አድርጎ ይመለከታል፤ ብዙውን ጊዜ እንዲህ ያሉትን ባህርያት የዕለት ተዕለት ኑሮ ጫናዎች እንዲሁም ሰዎች አድናቆት እንዲያተርፉና ተወዳጅ እንዲሆኑ የመፈለግ ዝንባሌ በማሳየት ያጎላቸዋል። ራስን ከመግዛት ባህርይ ዓይናችንን ስናዞር እና በድርጊታችንና በንግግራችን የመንፈስ ቅዱስን የዋህነትና መጠነኛነት ችላ ስንል፣ በቀላሉ በጠላት ወጥመድ ውስጥ እንወድቃለን፤ ይህም በማህበራዊ፣ በቤተሰብ አልፎ ተርፎም በቤተክርስቲያን መሪዎቻችን ግንኙነታችን ውስጥ ልናሳዝነው የምንችል ቃላትን እንድንናገርና አመለካከቶችን እንድንይዝ ያደርገናል። የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል በተለይ ፈታኝ ሁኔታዎች በሚያጋጥሙን ጊዜ ይህን በጎነት እንድናሳይ ይጋብዘናል፤ ምክንያቱም የግለሰብ እውነተኛ ባህርይ የሚገለጠው በእነዚህ ወቅቶች ነውና። ማርቲን ሉተር ኪንግ፣ ዳግማዊ በአንድ ወቅት እንዳሉት፣ “የአንድ ሰው የመጨረሻ መለኪያ በዐረፍት እና ምቾት ባላቸው ጊዜያት የሚቆምበት ሳይሆን በፈተና እና በአስቸጋሪ ጊዜ የሚቆምበት ነው።“

የቃል ኪዳኑ ሰዎች እንደመሆናችን መጠን፣ ለጌታ በሰጠናቸው የተቀደሱ ተስፋዎች ላይ ልባችንን አጥብቀን በመያዝ እንድንኖር ተጠርተናል፣ ይህን የምናደርገውም ፍጹም በሆነው ምሳሌው የሰጠንን ምሳሌ በጥንቃቄ በመከተል ነው። በምላሹም እንዲህ በማለት ቃል ገብቷል፣ “እውነት፣ እውነት እላችኋለሁ፣ ይህ የእኔ ትምህርት ነው፣ እናም በዚህም የሚገነባ በእኔ አለት ላይ መሰረቱን የገነባ፣ እናም የሲዖል ደጆችም አያሸንፋቸውም።”

አዳኝ

ልባችሁ አይታወክ [Let Not Your Heart Be Troubled], by Howard Lyon, courtesy of Havenlight

አዳኛችን በምድር ላይ ያከናወነው አገልግሎት በባህሪው በሁሉም ዘርፎች ራስን በመግዛት ባህርይ የተላበሰ ነበር። ፍጹም በሆነው ምሳሌው አማካኝነት “በስቃይ ታጋሽ ሁን፣ ክፉ ለሚናገሩህ ክፉ አትመል” ብሎ አስተምሮናል። በክርክርና በግጭት ምክንያት ለቍጣ መገዛት እንደሌለብን ሲያስተምር እንዲህ ብሏል፦ “ንስሐ ግቡና እንደ እንደህፃናት ሁኑ።” በተጨማሪም በሙሉ ልባቸው ወደ እሱ መምጣት የሚፈልጉ ሁሉ በቍጣ ከሚያዩአቸው ወይም በእነሱ ላይ የሆነ ነገር ካላቸው ሰዎች ጋር መታረቅ እንዳለባቸው አስተምሯል። በትዕግስትና በርኅራሄ የተሞላ ልብ በመያዝ ጨካኝ፣ ደግነት የጐደለው፣ አክብሮት የጐደለው ወይም ችላ የተባለ ነገር ቢያጋጥመን እንኳ፣ ቸርነቱ እንደማይለየን፣ የሰላም ቃል ኪዳኑም ከህይወታችን እንደማይወገድ አረጋግጦልናል።

ከጥቂት ዓመታት በፊት እኔና ባለቤቴ በሜክሲኮ ሲቲ ከሚገኙ አንዳንድ ታማኝ የቤተክርስቲያን አባላት ጋር የመገናኘት እድል አግኝተን ነበር። ብዙዎቹ በግላቸውም ሆኑ በሚወዷቸው ሰዎች አማካኝነት ሊገለፁ የማይችሉ ፈተናዎችን በፅናት ተቋቁመዋል፤ ከእነዚህም መካከል ጠለፋ፣ ግድያና ሌሎች ልብ የሚሰበሩ አሳዛኝ ክስተቶች ይገኙበታል።

የእነዚያን ቅዱሳን ፊቶች ስንመለከት ቍጣ፣ ቂም ወይም የበቀል ፍላጐት አላየንም። ይልቁንስ ዝምተኛ ትህትናን ተመልክተናል። ፊታቸው በኀዘን የተሞላ ቢሆንም፣ ለመፈወስና ለማጽናናት ያላቸውን ልባዊ ጕጕት ይገልጹ ነበር። እነዚህ ቅዱሳን በመከራ ልባቸው ቢሰበርም በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን ወደፊት ይገሰግሳሉ፣ መከራቸው በእምነታቸው ላይ ክፍተት እንዲፈጥር ወይም በወንጌል ምስክርነታቸው ላይ አለመረጋጋት እንዲፈጥር አልፈቅዱም።

በስብሰባው ማጠቃለያ ላይ ለእያንዳንዳቸው ሰላምታ አቅርበናል። እያንዳንዱ የእጅ መጨባበጥ፣ እያንዳንዱ እቅፍ፣ በጌታ እርዳታ፣ የህይወት ተስፋ አስቆራጭና ፈታኝ ሁኔታዎችን በቍጥጥር ሥር ለማዋል መምረጥ እንደምንችል የሚያሳይ ዝምተኛ ምስክርነት ሆነ። የፀጥታና የዋህነት ምሳሌነታቸው በሁሉም ነገር ራስን በመግዛት በአዳኙ ጐዳና ላይ እንድንጓዝ የሚያበረታታ ነበር። በመላእክት ፊት እንደሆንን ተሰማን።

ከሁሉ የሚበልጠው ኢየሱስ ክርስቶስ በእያንዳንዱ ቀዳዳው ደም እስኪፈሰስ ድረስ ስለ እኛ ተሰቃይቷል፤ ሆኖም ቍጣ ልቡን እንዲያቃጥል አልፈቀደም፤ እንዲሁም እንዲህ ባለው ሥቃይ ውስጥም እንኳ አረመኔያዊ፣ አጸያፊ ወይም ጸያፍ ቃላት ከከንፈሮቹ አላመለጡም። ፍጹም የሆነ ራስን የመግዛት ባህርይና ተወዳዳሪ የሌለው የዋህነት ስላለው፣ ስለራሱ ሳይሆን ስለ እያንዳንዳቸው የእግዚአብሔር ልጆች ማለትም ስለ ያለፉት፣ ስለአሁኑና ስለወደፊቱ ያስብ ነበር። ሐዋርያው ጴጥሮስ ስለ ክርስቶስ የላቀ አመለካከት ሲናገር እንዲህ ብሏል፦ “ሲሰድቡት መልሶ አልተሳደበም መከራንም ሲቀበል አልዛተም፥ ነገር ግን በጽድቅ ለሚፈርደው ራሱን አሳልፎ ሰጠ፤” አዳኛችን በከፍተኛ ሥቃይ ውስጥ በነበረበት ወቅት እንኳ ፍጹም የሆነ መለኰታዊ ራስን መግዛትን አሳይቷል። “ሆኖም፣ ለአብ ክብር ይሁን፣ እናም ጠጥቼዋለሁ እናም ለሰዎች ልጆችም ዝግጅቴን ጨርሻለሁ” በማለት አውጇል።

የተወደዳችሁ ወንድሞቼና እኅቶቼ የፕሬዚዳንት ራስል ኤም ኔልሰን የትንቢታዊ ጥሪ ቅዱስ ምላሽ እንደመሆኑ መጠን ልባችንንና አዕምሮአችንን በክርስቲያናዊ ራስን የመግዛት ባሕርይ እንድናጌጥ ከልብ እጋብዛችኋለሁ። በድርጊታችንና በንግግራችን ራስን የመግዛት ባህርይን ለመቅረጽ በእምነትና በትጋት ስንጥር ህይወታችንን በአዳኛችን አስተማማኝ መሠረት ላይ ይበልጥ አጠንክረን እናሳርፋለን ብዬ እመሰክራለሁ።

የማያቋርጥ ራስን መግዛት ጥረት ነፍሳችንን እንደሚያነጻና ልባችንን በአዳኛችን ፊት እንደሚቀድስ፣ ቀስ በቀስ ወደ እርሱ እንድንቀርብ እና በተስፋ እና በሰላም እርሱን በዳግም ምጽዓቱ በምንገናኝበት ክብራማ ቀን እንድናዘጋጅ እንደሚያድርገን እመሰክራለሁ። እነዚህን ቅዱስ ቃላት በአዳኛችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እጋራቸዋለሁ፣ አሜን።